Saturday, September 5, 2015

“በመካሪነት በኩል ሞት በቃ!” ይባል ነበር ድሮ



“በመካሪነት በኩል ሞት በቃ!” ይባል ነበር ድሮ

(ኢብኑ ሙነወር፣ ነሀሴ 26/2007)
 

ድሮ ድሮ ዘመድ ወዳጅ ሲሞት አገር ሁሉ ያዝን ይጨነቅ ነበር፡፡ የአንዱን ወዳጅ ሞት ተከትሎ የሞትን አስፈሪነት፣ የዱንያን አላቂነት እዚህም እዚያም የሚያወሳው ስለሚበዛ አዋቂ ቀርቶ ልጆች እንኳን ሳይቀሩ ከውስጣቸው ፍርሃት ይሰፍን ነበር፡፡ አንድ ሰው ጣእረ-ሞት ላይ መሆኑ ሲሰማ አገር ይጨነቃል፡፡ ሞቱ ሲሰማ ደግሞ አገር በድንጋጤ ይዋጣል፡፡ ከቀብር መልስ ደግሞ ሌላ የሀዘን ድባብ፣ ሌላ “ዋ! መጨረሻችን፡፡” የቀብር ጥያቄን፣ የቂያማ አስፈሪ ሁኔታን እያሰላሰለ በስጋት የሚዋጠው ቀላል አልነበረም፡፡ የዘነጋ ካለም በትንሽ ማስታወሻ ቅስሙ ይሰበራል፣ በድንጋጤ ይዋጣል፣ ውስጡ ሁሉ ይረበሻል፡፡ ለአፍታም ቢሆን ባለበት ሁኔታ ሞት ድንገት “እጅ ወደላይ” እንዳይለው በመስጋት ወደ ጌታው ይመለሳል፣ ዐውፍ ይባባላል፣ አማናን ይመልሳል፣ ሶላቱን እንደ አዲስ ይጀምራል፣ ሌላም ሌላም፡፡ ዛሬ ግን ትላንት አይደለም፡፡ ሞት ባይቀርም ሞትን ተከትሎ መቶበት ግን ምናልባት ካልቀረ ቀሏል፡፡ ሞት ቢበዛም በሞት አኺራን ማስታወስ ግን መንምኗል፡፡ ወዳጃችንን፣ ወገናችንን ከዒባዳው አለም ከፈተናው አለም ወደ ደሞዝ አለም፣ ወደ ጥያቄው አለም እየሸኘነው እንኳን ቡድን ቡድን ሰርተን እናሽካካለን፣ ምንም እንዳልተፈጠረ፣ ምንም እንደማይጠብቀን፣ ያለ ይሉኝታ፣ ያለ ሐያእ፣ እናወራለን፣ እናወራለን፣ እናወራለን፡፡ እያወራንም እንገለፍጣለን፡፡ አስከሬን ከአፈር በታች እየገባም ያለምንም “ነግ በኔ” ድምፃችንን ከፍ አድርገን ከጓደኛ ጋር ወይም በስልክ ስለ ቢዝነስ እናወራለን፣ ቢዝነስ! ቆመን ተቀምጠን ቢዝነስ! እየሰገድን የምናስበው ቢዝነስ! ስንተኛ ስንነሳ እንደ ዚክር የሚታወሰን ቢዝነስ! ወደ ሀብት እሽቅድድም!! ሀያሉ “በብዛት መፎካከር (ጌታችሁን ከመገዛት) አዘናጋችሁ፡፡ መቃብሮችን እስከምትጎበኙ (እስከምትሞቱ) ድረስ” ማለቱ ምንኛ አስፈሪ ሐቅ ነው፡፡ “ተከልከሉ” እያለ ነበር፡፡ ግና ማን ይስማ? ልብ ከተዘጋ ጆሮ በድን ነው፡፡
ሱብሓነላህ! መዘናጋታችን እጅጉን ለከት አጥቷል፡፡ ሞቱ የራሳችን የቤተሰባችን ከሆነም የወግ የባህሉ እንዳይቀር ስለተለየን ስጋ ዋይታ ከማሰማታችን ባለፈ ለሸሪዐው ህግና ደንብ እጅ የምንሰጠው ስንቶቻችን ነን? በሱናው አናካትምም፣ በሱናው አንገንዝም፣ በሱናው አንሰግድም፣ በሱናው አንደፍንም፣ በሱናው አንፅናናም፡፡ አዎ እነዚህ ነገሮች በአብዛሀኛው እንዳሉን ይገባኛል፡፡ ነገር ግን ላቀበሉን አባቶች አላህ ውለታቸውን ይክፈላቸውና በውርስ ከመቀበላችን ውጭ በውስጣቸው ስለሚገኙ እርማት ስለሚሹ ነገሮች ግን ትኩረታችንም አይደለም፡፡ ማካተሙን፣ መገነዙን፣ መድፈኑን ወዘተ በኪታብ ከሚቀራውና ከሚያስተምረው ቃልቻ ይልቅ በውርስ ያገኘው የኔ ብጤ ጃሂል ነው በአብዛሀኛው የሚያከናውነው፡፡
ወደ ነገሬ ስመለስ ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እንዳሉት ዛሬ ሞት እጅጉን በዝቷል፡፡ ሰው ዛሬ በየእለቱ እንደቅጠል ይረግፋል፡፡ እያወራ ይሞታል፣ እየሄደ ይሞታል፣ በተኛበት ይሞታል፣ ስሙ እጅጉን በበረከተ የህመም አይነት ይሞታል፣ እንደ ዋዛ ከቤቱ ወጥቶ ይቀራል፡፡ የዜና አውታሮች አብዛሀኛው ሽፋናቸው ሞት ነው- አይነቱ የበዛ እልቂት፡፡ እጅጉን ከመብዛቱ፣ በዱንያም ከመጠመዳችን የተነሳ ጆሯችን በሞት ዜና አይሳቀቅም፡፡ ልባችንም ደንድኗል አይደነግጥም፡፡ ግና ከመብዛቱ የተነሳ ብዙም ሳይደንቀን የምንሰማው ሞት ከአፍታ ወይም ከዘመናት በኋላ ተረኞች እንንደምንሆንበት እሙን ነው፡፡
እርግጥ ነው በዱንያ መልካምን የሚሰራ፣ ለበጎ ስራ የሚታትር፣ ለኢኽላስ የሚጨነቅ፣ ጧት ማታ ጌታውን የሚያወሳ አካል ሞትን አይፈራም፣ አይጠላውምም፡፡ ምክንያቱም በሞት እርባና ቢሷን ዱንያ ተሰናብቶ ዘላለማዊቷን ሀገር ያልማልና፡፡ ሞትን አይፈራም፡፡ ከፀጋዎች ሁሉ በላጭ ፀጋ የሆነውን ጌታውን መመልከትን ይናፍቃልና፡፡
ነገር ግን የቂናችን በመድከሙ፣ የዱንያ ፍቅራችን በማየሉ፣ ለመኖር ያለን ጉጉት ወሰን አልባ በመሆኑ ሳቢያ ሞትን እንጠላለን፡፡ ስለምንጠላም እውነተኛው አይቀሬው ሞት ከመምጣቱ በፊት ብዙ ጊዜ እንሞታል፡፡ አዎ ደግመን ደጋግመን በጭስ አልባ ሽብር እንሞታለን፡፡ በሽብር እንደ ጨው እንሟሟለን፣ እንደ በረዶ እንቀልጣለን፡፡ ሽብር ስል አጥፍቶ መጥፋት ማለቴ አይደለም። ሽብር ማለቴ ስለ አይ ኤስ ወይም አልቃኢዳም አይደለም። የማወራው ከአይኤስ ከአልቃኢዳ የሚያስከነዳ ሽብር እየፈፀሙ በሽብር ስም ስለሚነግዱት እስራኤል፣ አሜሪካና ተባባሪዎቻቸውም አይደለም። ሽብር ስል እያሸበሩ በሽብር ስለሚነግዱትም አይደለም፡፡ የማወራው ለዱንያ ያለን ፍቅር ገደብ በማጣቱ ሳቢያ የእያንዳንዳችንን ቤት እያንኳኳ ስላለው ሽብር ነው። የማነሳው ሞትን እጅጉን ከመጥላታችን የተነሳ እያርበደበደን ስላለው ሽብር ነው። አዎ አንድ ጥይት ሳይተኮስ አንድ ቦንብ ሳይፈነዳ በፍርሃት እያራደን ያለው ሽብር። ይሄኛው ሽብር ዘር ከሃይማኖት አይመርጥም። ይሄኛው ሽብር በሰው አልባ ድሮን በብረት ለበስ ታንክ አይወደምም። ይሄኛውን ሽብር ጓንታናሞ አቡ ገሪብ አስገብቶ ቁም ስቅሉን ማሳየት አይቻልም። ይሄኛው ሽብር በተቀነባበረ ክስ በሀሰት ምስክርም አይገላገሉትም።
አሸባሪው ገና ከርቀት ስናየው በስጋት መንገድ የምንለቅለት ቀይ ሽብሩ ሲኖ ትራክ (ሲኖ ጭራቅ) አይደለም። ሽብሩ ደም ግፊት ነው፣ እስትሮክ ነው። ሽብሩ ካንሰር ነው፣ የስኳር ህመም ነው፣ ኤች አይ ቪ ኤድስ ነው። ሽብሩ ጉበት ነው ኩላሊት ነው። ዛሬ “የጉበት ህመም አለብህ” ስለተባለ ብቻ የጨው አምድ የሚሆነው ቀላል አይደለም፡፡ ዛሬ “ካንሰር አለብህ” ስለተባለ ብቻ ተስፋ ቆርጦ እራሱን የሚያጠፋው ጥቂት አይደለም፡፡ ዛሬ “ስኳር አለብህ” ስለተባለ ብቻ የሚያየው ሁሉ ጨለማ የሚሆንበት አንድ ሁለት አይደለም፡፡ ታዲያ ከዚህ በላይ ምን ሞት አለ? የትኛውስ በሽታ ባይይዝህ ሞት ሊቀር ነውን? ታዲያ ይሄ ሁሉ ሽብር፣ ይሄ ሁሉ ተስፋ መቁረጥ ለምን? “ሞት ላይቀር ማንቋረር” ያለው ማን ነበር? አትጠራጠር ሞት ሁሉም የሚጎነጨው ፅዋ ነው። የሞትከው የተወለድከ እለት ነው፡፡ አለቀ!! ጌታችን አላህ፡ “ነፍስ ሁሉ ሞትን ቀማሽ ናት።” “የትም ብትሆኑ በጠነከሩ ህንፃዎች ውስጥ ብትሆኑም እንኳን ሞት ያገኛችኋል” ይላል፡፡ ይልቅ የዘነጋነው ሌላ ሞት አግኝቶናል፡፡ ይልቅ ያላስተዋልነው ሌላ ሙሲባ ወድቆብናል፡፡ መልክና አምሳያ የሌለው ሞት!! የልብ ሞት!! ከዚህ በላይ ምን ሞት አለ? ሱፍያን አሥሠውሪይ ረሒመሁላህ “በሰዎች ላይ ልቦች ሞተው አካላት ህያው የሚሆኑበት ዘመን ይመጣል” ይላሉ፡፡ አላሁልሙስተዓን!! ይሄው ልባችን ሞቶ በድናችን ቀርቷል፡፡ ኢና ሊላሂ ወኢና ኢለይሂ ራጂዑን! “ለአኺራየስ ምን ተዘጋጅቻለሁ?” ብሎ በመጨነቅ ፋንታ ቀልባችንን ለገደለችው ዱንያ ስንል ተስፋ እንቆርጣለን፡፡ ሌላ ሞት፡፡ እራስን ማጥፋት!! ብልጦች እንደሆንን እናስባለን፡፡ ግና ሲበዛ ቂሎች ነን፡፡ ከዘላለማዊ ህይወቱ ይልቅ አላፊ ቆይታን ካስቀደመ ሰው በላይ ማን ቂል አለ?! “ብልጥማ እራሱን የተቆጣጠረው ነው፣ ከሞት በኋላ ላለ ህይወቱ የተጋው፡፡”
ድሮ ከታላላቆቹ ሶሐብዮች ዐብዱላህ ኢብኒ መስዑድ እና ዐማር ኢብኑ ያሲር ረዲየላሁ ዐንሁማ ተይዞ "ከመካሪነት በኩል ሞት በቃ!" የሚል ልብን ዘልቆ የሚነካ መልእክት ተላልፎ ነበር። በርግጥ ሰነዱ ዶዒፍ መሆኑ እንጂ ከነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም በማገናኘትም የተላለፈበት አለ። ዝርዝረሩን የሸይኹልአልባኒን ረሒመሁላህ አድዶዒፋህ ኪታብ ቁጥር: 502 ይመልከቱ። ብቻ ከሶሐቦቹ የተገኘው ትውፊት ለመማማር በቂያችን ነው። እውነትም እንደሞት ማን መካሪ ነበር!? ሞት ያላስተማረው ሰው በምን ይማራል? ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም "ጥፍጥናዎችን ቆራጭ የሆነውን (ሞትን) ማስታወስን አብዙ" ማለታቸው ለዋዛ አልነበረም። ምን ዋጋ አለው ዛሬ ከሞትም የምንማረው ጥቂቶች ሆነናል። በቤተሰባችን፣ በጓደኛችን ሞት ከማዘን ከማንባት በዘለለ "ድንገት ተረኛ ብሆንስ?" ብለን ተጨንቀን ላፍታ እንኳን የቀብር ህይወትን፣ ቂያማን፣ ሲራጥን፣ ሚዛንን ወዘተ አስታውሰን በመዘናጋታችን የደነገጥነው ከሰመመናችን የነቃነው ስንቶቻች ነን?
እኩይ ምግባርን ባህሪህ ያደረግከው ወገኔ ሆይ ከፊትህ ሞት አለ። የሰው ሐቅ ያለ አግባብ የምትነጥቀው ብልጥ መሳዩ ቂል ሆይ ከፊትህ ሞት ተደቅኗል። ሃሜተኛው ነገረኛው ፍጥረት ሆይ የስራህን ታጭድ ዘንድ ሞት ከፊትህ እየጠበቀህ ነው። በሶላትህ የምትቀልደው የምትዘናጋው ቦዘኔ ሆይ! ዘላለማዊ ቁጭትን የሚያወርስህ ሞት ተደግሶልሃል። የወላጆችህን ሐቅ የምትጥሰው አደራ በላ ሆይ ዛሬ ነገ ሳትል በፍጥነት እራስህን አስተካክል፣ ከጌታህ ጋር ታረቅ፡፡ በጥቅሉ ለጌታህ ለዲንህ ጀርባህን የሰጠኸው ዝንጉ ሆይ! ሞት ወደ አንተ እየመጣ ነው፡፡ ወንድሜ ሆይ እህቴ ሆይ ወደ ጌታችን እንመለስ፡፡ ጧት ማታ ሞትን እናስታውስ፡፡ አንዱ ዓሊም እንዲህ ይላሉ፡ “ሞትን ማስታወስን ያበዛ ሰው ሶስት ነገሮችን ይታደላል፡፡ እነሱም ተውባን ማፋጠን፣ የልብ መብቃቃት እና ለዒባዳህ መነሳሳት፡፡ ሞትን የረሳ ደግሞ በሶስት ነገሮች ይቀጣል፡፡ ተውባን እየተዘናጉ ማሳለፍ፣ ባለ አለመብቃቃት እና ከዒባዳህ መዘናጋት፡፡” እስኪ እራሳችንን እንገምግም፡፡ ሞት አማክሮ አይመጣምና በተጠንቀቅም እንሁን፡፡ ኢብኑ ዑመር ረዲየላሁ ዐንሁ “ካመሸህ ንጋትን አትጠባበቅ፡፡ ካነጋህ ደግሞ ምሽትን አትጠባበቅ፡፡ በጤናህ ጊዜም ለህመምህ ጊዜ የሚሆንህን፤ በህይወት ሳለህም ስትሞት የሚሆንህን ያዝ” ይላሉ፡፡ በጥፋት የምንጠምዳቸው የአካል ክፍሎቻችን በኛ ላይ ምስክር ከመሆናቸው በፊት እንንቃ፡፡ ሞት የትና መቼ እንደሚይዘን አናውቅምና አዋዋላችንን እናሳምር፣ ባስቸኳይ ወደ አላህ እንመለስ፡፡ ጌታዬ ሆይ ይቅር በለን። አንተን በማስታወስ፣ አንተን በማመስገን፣ አንተን ባማረ መልኩ በመገዛትም ላይ አግዘን።
አንተ የቆምከው ከቀብሬ
አትደነቅ በነገሬ
እንዳንተው ነበርኩኝ ትላንት
የዘነጋሁ ከዚህ መዐት
ይልቅ ተመከር አንሰራራ
ነገ አንተ ነህ ባለ ተራ፡፡

(ኢብኑ ሙነወር፣ ነሀሴ 26/2007)