Friday, April 1, 2016

አንድ ባል የወር አበባ ደም ላይ ካለች ሚስቱ ጋር ግንኙነት መፈፀም እንደማይችል የምናውቀው ስንቶቻችን እንሆን? ጥፋቱስ ከተፈፀመ ማካካሻው ምንድን ነው?

(ኢብኑ ሙነወር፣ ነሐሴ 15/2007)

አንድ ባል የወር አበባ ደም ላይ ካለች ሚስቱ ጋር ግንኙነት መፈፀም እንደማይችል የምናውቀው ስንቶቻችን እንሆን? ጥፋቱስ ከተፈፀመ ማካካሻው ምንድን ነው?

1. ብይኑ
በወር አበባ ወቅት የግብረ-ስጋ ግንኙነት መፈፀም በጥብቅ የተከለከለ አደገኛ ወንጀል ነው፡፡ ጌታችን አላህ እንዲህ ይላል፡-
وَيَسْأَلُونَكَ عَنِ الْمَحِيضِ قُلْ هُوَ أَذًى فَاعْتَزِلُوا النِّسَاءَ فِي الْمَحِيضِ وَلَا تَقْرَبُوهُنَّ حَتَّى يَطْهُرْنَ فَإِذَا تَطَهَّرْنَ فَأْتُوهُنَّ مِنْ حَيْثُ أَمَرَكُمُ اللَّهُ إِنَّ اللَّهَ يُحِبُّ التَّوَّابِينَ وَيُحِبُّ الْمُتَطَهِّرِينَ (222)
“ስለ የወር አበባ ደም ይጠይቁሃል፡፡ ‘እርሱ አስፀያፊ ነገር ነው፡፡ ስለሆነም ሴቶችን በወር አበባ ጊዜ (ከመገናኘት) ራቋቸው፡፡ ንፁህ እስከሚሆኑም ድረስ አትቅረቧቸው፡፡ ንፁህ በሆኑም ጊዜ አላህ ካዘዛችሁ ስፍራ ተገናኟቸው፡፡ አላህ ተመላሾችን ይወዳል፤ ተጥራሪዎችንም ይወዳል’ በላቸው፡፡” [አልበቀራህ፡ 222]
ነብዩም ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም፡- “የወር አበባ ደም ላይ ያለችን ሴት የተገናኘ ወይም ሴትን በፊንጢጣዋ የተገናኘ ወይም ከጠንቋይ ዘንድ የሄደ ሰው በሙሐመድ ላይ በወረደው ክዷል” ይላሉ፡፡ ሐዲሡን አልባኒ “ሶሒሕ” ብለውታል፡፡ [ሶሒሑትተርጊብ ወትተርሂብ፡ 2433]
2. በወር አበባ ጊዜ ግንኙነት ከተፈፀመ የጥፋቱ ማካካሻው ምንድን ነው?
በዚህ ግንኙነት በማይፈቀድበት ወቅት ላይ ግንኙነት የፈፀመ ሰው ከባድ ጥፋት ፈፅሟል፡፡ ለጥፋቱ ማበሻ ይሆነውም ዘንድ አንድ ዲናር ወይም ግማሽ ዲናር ሊመፀውት እንደሚገባ ነብያችን ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ደንግገዋል፡፡ [ሶሒሕ አቢ ዳውድ፡ 257] አንድ ዲናር ማለት 4.25 ግራም ወርቅ ሲሆን ግማሹ ደግሞ 2.125 ግራም ነው፡፡ እናም በዚህ ጊዜ ግብረ-ስጋ ግንኙነት የፈፀመ ሰው ይህን ያክል ይሰድቃል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የዘመኑ የአንድ ግራም ወርቅ ዋጋ ለምሳሌ 800 ብር ቢሆን 4.25 x 800= 3,400 ብር ወይም ደግሞ የዚህን ግማሽ 2.125 x 800=1,700 ብር ሊሰድቅ ይገባል ማለት ነው፡፡
እንግዲህ ተመልከቱ አንድ ሰው አንዴ ለፈፀመው ህገ-ወጥ ግንኙነት ቅጣት ይሆን ዘንድ ይህን ያክል ገንዘብ አንዴ ባግባቡ ቢያወጣ ዳግም ወደዚህ ጥፋት የመመለስ እድሉ በጅጉ ይጠብ ነበር፡፡ ነገር ግን ህጉን ባለማወቃችን ወይም ደግሞ የጥፋቱን ክብደትና ማካካሻውን ጠንቅቀን ባለመረዳታችን ምክንያት ስንቶቻችን ነን በወንጀል የምንጨማለቀው?! አላህ ድንጋጌዎቹን የምንረዳ ለህጉ የምናድር ያድርገን፡፡
ሸይኹልአልባኒ ረሒመሁላህ እንዲህ ይላሉ፡ “ነፍሱ አሸንፋው የወር አበባ ላይ ያለችን ሴት ከደሟ ከመጥራቷ በፊት የተገናኘ ሰው በሱ ላይ አቅራብ በሆነ ስሌት ግማሽ የእንግሊዝ ፓውንድ ወርቅ ወይም እሩቡን የመመፅወት ግዴታ አለበት፡፡ ይህም ዐብዱላህ ኢብኒ ዐባስ ከነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ያስተላለፈውን የወር አበባ ላይ ሳለች ሚስቱን ስለሚገናኝ ሰው “በአንድ ዲናር ወይም በግማሽ ዲናር ይሰድቅ” ሲሉ የተናገሩትን ሐዲሥ መነሻ በማድረግ ነው፡፡ … ምናልባትም በአንድ ዲናር ወይም በግማሹ ተብሎ አማራጭ መሰጠቱ ወደ መፅዋቹ የአቅም ሁኔታ የሚመለስ ሊሆን ይችላል፡፡ ምንም እንኳን ሰነዳቸው ደካማ ቢሆንም የሐዲሡ አንዳንድ ዘገባዎች ይህን ያመላክታሉ፣ ወላሁ አዕለም፡፡” [አዳቡዝዚፋፍ፡ 50]
3. ግን ለምን በወር አበባ ጊዜ ግነኙነት ተከለከለ?
በዚህ ሰአት ግንኙነት መፈፀሙ አስፀያፊ መሆኑ ህሊናው ላልታወረ ሁሉ አይሰወርም፡፡ ከዚያም ባለፈ የራሱ የሆነ ጉዳት አለው፡፡ ደረጃው ቢለያይም ለወንዱም ለሴቷም የጎንዮሽ ጉዳት እንዳለው ምሁራን ይገልፃሉ፡፡ ብዙ ሴቶች የወር አበባ ላይ ሲሆኑ ለአእምሮ አለመረጋጋት፣ ብስጭት፣ ድብርት፣ የጀርባ ህመም፣ የሆድ ቁርጠት፣ ማቅለሽለሽ፣ ድካም፣ ራስ ምታትና መሰል ህመሞች ያጋጥሟቸዋል፡፡ የእለት ከእለት ስራዎቻቸውን ለማከናወን የሚያቅታቸው ሁሉ አሉ፡፡ እናም የወር አበባ ኡደታዊ ደም ወቅታዊ ቢሆኑም የተለያዩ ማህበራዊና ስነ ልቦናዊ ጫናዎችን ያሳድራል፡፡ በዚህ ሁኔታ ላይ ግንኙነት መፈፀም በተለይም ሴቷ ላይ ይበልጥ ችግር መፍጠር፣ ይበልጥ ስቃይን መጨመር ነው፡፡ በዚያ ላይ ማህፀን አካባቢ እራሱን የቻለ የህመም ስሜት አለ፡፡ በዚህ ሰአት ማህፀንና አካባቢው ከወትሮው በተለየ መልኩ የመኮማተርና የመድከም ባህሪ ስለሚኖረው ባእድና ውጫዊ አካል ካገኘው የመቁሰል፣ በኢንፌክሽን የመጠቃት፣ ለተጨማሪ ህመም የመጋለጥ እድሉ ሰፊ ነው፡፡
4. በወር አበባ ወቅት ባል ከሚስቱ የሚፈቀድለት ምንድን ነው?
በወር አበባ ወቅት የሩካቤ ስጋ ግንኙነት እንጂ አብሮ መብላት፣ መጠጣት፣ መቀመጥ አልተከለከለም፡፡ ኢስላም በዚህ ረገድ የተለየ ህግ አለው፡፡ በክርስትና በወር አበባ ወቅት ሴቷ እሷ ብቻ ሳትሆን የነካትም ጭምር የረከሰ ነው፡፡ "ሴት ጊዜዉን እየጠበቀ የሚመጣ የደም መፍሰስ ቢኖርባት የወር አበባዋን ርኩሰት እስከ ሰባት ቀን ይቆያል፡፡ #በዚህ_ጊዜ #ማንም_ሰዉ_ቢነካት እስከ ማታ ድረስ #እርኩስ ይሆናል፡፡ በወር አበባዋ ጊዜ #የምትተኛበት_ነገር #ማንኛዉም_ነገር_እርኩስ_ይሆናል፡፡ #የተቀመጠችበትን_ማንኛዉም ነገር #የነካ_ሰዉ ልብሱን ይጠብ ሰዉነቱንም ይታጠብ #እስከ_ማታ_ድረስ_ግን #እርኩስ_ይሆናል" ይላል መፅሀፋቸው፡፡ [ዘሌዋዉያን 15: 19-22] አይሁዶችም ዘንድ ያለው ሁኔታ ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ አነስ ኢብኑ ማሊክ ረዲየላሁ ዐንሁ እንዲህ ይላሉ፡ “የሁዶች ከነሱ አንዲት ሴት የወር አበባ ካየች ከቤት ያስወጧት ነበር፡፡ አብረዋት አይበሉም፣ አብረዋትም አይጠጡም፣ በቤቶቻቸውም ውስጥ አብረዋት አይቀላቀሉም ነበር፡፡ የአላህ መልእክተኛ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ስለዚህ ሲጠየቁ የጠራው አላህ ‘ስለ የወር አበባ ደም ይጠይቁሃል፡፡ እርሱ አስፀያፊ ነገር ነው፡፡ ስለሆነም ሴቶችን በወር አበባ ጊዜ (ከመገናኘት) ራቋቸው’ የሚለውን እስከመጨረሻው አወረደ፡፡ የአላህ መልእክተኛም ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ‘በቤቶቻችሁ ውስጥ ተቀላቀሏቸው፡፡ የሩካቤ ስጋ ግንኙነት ሲቀር ሁሉንም ነገር ፈፅሙ’ አሉ፡፡ የሁዶች ይህ ነገር ሲደርሳቸው ‘ይሄ ሰውየ ከኛ ጉዳይ ውስጥ የሚፃረር ቢሆን እንጂ አንድም ነገር አልቀረውም!!’ አሉ፡፡...” [ሶሒሕ አቢ ዳውድ]
ስለዚህ ሸሪዐችን በወር አበባ ወቅት ሴቶችን በምግብ፣ በመኝታና መሰል ነገሮች ማግለልን አያስተምርም፡፡ ደሙ በራሱ ቆሻሻ ቢሆንም ከዚያ ባለፈ ሌሎች ዘንድ እንደሚስተዋለው መላ አካሏን የነካትን ነገር ሁሉ የረከሰ ነው አንልም፡፡ ያሳለፍነው ማስረጃ በቂ ቢሆንም ለማጠናከር ያክል ጥቂት እንጨምር
- በአንድ ወቅት ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም “ዓኢሻ ሆይ! እሱን ልብስ አቀብይኝ” ሲሏት “የወር አበባ ላይ ነኝ” አለቻቸው፡፡ ይህኔ እሳቸው “የወር አበባሽ ከእጅሽ ላይ አይደለም” አሏት፡፡ [ሙስሊም] መይሙናም ረዲየላሁ ዐንሃ ባለቤቷ ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም የወር አበባ ላይ እያለች አብረዋት ይተኙ እንደነበር ገልፃለች፡፡ [ሙስሊም] ኡሙ ሰለማህ ባስተላለፈችው ደግሞ “በአንድ ወቅት ከአላህ መልእክተኛ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ጋር ጋቢ ለብሼ ተኝቼ ሳለሁ የወር አበባየ መጣብኝና ቀስ ብየ ወጣሁኝና የወር አበባ ልብሴን ያዝኩኝ፡፡ የአላህ መልእክተኛ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ‘የወር አበባሽ መጣ?’ አሉኝ፡፡ ‘አዎ’ አልኳቸው፡፡ ከዚያም ጠሩኝና በጋቢው ውስጥ አብሬያቸው ተኛሁኝ፡፡” [ቡኻሪና ሙስሊም]
- እናታችን ዓኢሻ ረዲየላሁ ዐንሃ “የወር አበባ ላይ ሆኜ የአላህ መልእክተኛን ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እራሳቸውን አጥብ ነበር”፣ “ፀጉራቸውን አበጥር ነበር” ትላለች፡፡ [ቡኻሪና ሙስሊም]፣ [ቡኻሪ]
- ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም የወር አበባ ላይ ካለች ሚስታቸው ጋር አብረው ይበሉና ይጠጡ ነበር፣ ኧረ እንዳውም ከዚያም በላይ!! ዓኢሻህ ረዲየላሁ ዐንሃ እንዲህ ትላለች “የወር አበባ ላይ እያለሁ እጠጣና ከዚያም ለነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም (መጠጫውን) አቀብላቸው ነበር፡፡ እሳቸውም አፋቸውን አፌን ካሳረፍኩበት ቦታ ላይ አድርገው ይጠጡ ነበር፡፡ የወር አበባ ላይ ሆኜ አጥንት እግጥና ከዚያም ለነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አቀብላቸዋለሁ፡፡ እሳቸውም አፋቸውን አፌ ካረፈበት ቦታ ያደርጉ ነበር፡፡” [ሙስሊም]
- እንዳውም የወር አበባ ላይ ካለች ሚስታቸው እቅፍ ስር ሆነው የተከበረውን ቁርኣን ያነቡ ነበር፡፡ እናታችን ዓኢሻህ እንዲህ ትላለች፡- “(ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም) እኔ የወር አበባ ላይ ሆኜ ከእቅፌ ውስጥ ይደገፉ ነበር፡፡ ከዚያም ቁርኣን ይቀሩ ነበር፡፡” [ቡኻሪና ሙስሊም] “ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እኔ የወር አበባ ላይ እያለሁ ከጎናቸው ተኝቼ ይሰግዱ ነበር፡፡ ሱጁድ ሲወርዱ ልብሳቸው ይነካኝ ነበር” ትላለች፡፡ [ቡኻሪ]
- ባጭሩ ከላይ እንዳሳለፍነው ከግብረ-ስጋ ግንኙነት ውጭ ሁሉም ነገር ይፈቀዳል፡፡ እናም ብልት በሚገባ ከተሸፈነ ያሰኘውን ከሚስቱ ጋር መጫወትና መጣቀም ይችላል ማለት ነው፡፡ ኢብኑ ቁዳማህ ረሒመሁላህ “የደሙ ቦታ በክልከላ መለየቱ ከሱ ውጭ ባሉት የተፈቀደ መሆኑን ጠቋሚ ነው” ይላሉ፡፡ [አልሙግኒ፡ 1/415] ይህ ማለት ግን በፊንጢጣ ግንኙነት መፈፀም ይፈቀዳል ማለት አይደለም፣ ነዑዙቢላህ! ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም “ሴትን በፊንጢጣዋ የተገናኘ የተረገመ ነው!” ብለዋልና፡፡ [ሱነን አቢ ዳውድ፡ 2162] በተጨማሪም “…ሴትን በፊንጢጣዋ የተገናኘ ወይም ከጠንቋይ ዘንድ የሄደ ሰው በሙሐመድ ላይ በወረደው ክዷል” ብለዋልና፡፡ [ሶሒሑትተርጊብ ወትተርሂብ፡ 2433]
ማሳሰቢያ፡-
የወር አበባን የሚመለከተው ብይን የወሊድ ደምንም በተመሳሳይ ይመለከታል፡፡ ኢብኑ ቁዳማህ ረሒመሁላህ “የወሊድ ደም ላይ ያሉም ልክ የወር አበባ ላይ እንዳለችዋ ነው የሚታዩት በዚህ ረገድ” ይላሉ፡፡ [አልሙግኒ፡ 1/419] ወላሁ አዕለም፡፡ ሼር ማድረግ አይርሱ፡፡ ሌሎችን ከጥፋት ይታደጉ፡፡

(ኢብኑ ሙነወር፣ ነሐሴ 15/2007)

Tuesday, March 15, 2016

9ኛ ሓዲስ:በአቅማችን ልክ እንደታዘዝን እና ልዩነትን ከማምጣት እንደተከለከልን።

الحديث التاسع

التكليف بما يستطاع والنهي عن الاختلاف

عَنْ أَبِي هُرَيْرَةَ عَبْدِ الرَّحْمَنِ بْنِ صَخْرٍ  قَالَ: سَمِعْت رَسُولَ اللَّهِ صلى الله عليه وسلم يَقُولُ: "مَا نَهَيْتُكُمْ عَنْهُ فَاجْتَنِبُوهُ، وَمَا أَمَرْتُكُمْ بِهِ فَأْتُوا مِنْهُ مَا اسْتَطَعْتُمْ، فَإِنَّمَا أَهْلَكَ الَّذِينَ مِنْ قَبْلِكُمْ كَثْرَةُ مَسَائِلِهِمْ وَاخْتِلَافُهُمْ عَلَى أَنْبِيَائِهِمْ ".
رَوَاهُ الْبُخَارِيُّ [رقم:7288]، وَمُسْلِمٌ [رقم:1337].

9ኛ  ሓዲስ

የሓዲሱ ትርጉም

በአቅማችን ልክ እንደታዘዝን እና ልዩነትን ከማምጣት እንደተከለከልን።

አቡ ሁረይራ  የአላህ መልእክተኛ صلى الله عليه وسلمእንዲህ ሲሉ ሰምቻቸዋሎህ አለ። “ የከለከልኳቹሁን ሁሉ ተከልከሉ። ካዘዝኳቹህ ውስጥ ደግሞ የቻላችሁትን ስሩ። ከናንተ በፊት የነበሩትን ህዝቦች ያጠፋቸውኮ ጥያቄ ማብዛታቸው እና ከብዮቻቸው መለያየታቸው ነው።”
ሓዲሱን ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል።

ከዘጠነኛው ሓዲስ የምንወስዳቸው ትምህርቶች

1. በቁርንአን እና በሓዲስ ከተከለከልነው ነገር መራቅ እንዳለብን።
2. በቁርአን እና በሓዲስ የታዘዝነውን ነገር የቻልነውን ያክል መስራት እንዳለብን።
3. ዲናችን(ሃይማኖታችን) ከአቅማችን በላይ የሆነን ነገር(የማንችለውን) እንድንሰራ እንደማያስገድደን።
4. የሚያስፈልገውን ጥያቄ ብቻ መጠየቅ እና ዝምብለን ጥያቄ ማብዛት እንደሌለብን(በተለይ ደግሞ በዋሒ ግዜ)።
5. ነብያት ላይ ጥያቄ ማብዛት እና ካመጡት ነገር መለየት(አለመከተል) ጥመትን እና ጥፋትን እንደሚያመጣ።

Saturday, February 6, 2016

የቁርኣን ሰዎች

ከ ወንድም Ibnu Munewor የተወሰደ።

ሸይኽ ሳሊሕ አልፈውዛን እንዲህ ይላሉ: "የቁርኣን ሰዎች ሲባል የሚፈለገው የሚያፍዙት፣ በሥርዓት የሚያነቡት ወዘተ ••• ማለት አይደለም። የቁርኣን ሰዎች የሚባሉት ባያፍዙት እንኳን የሚሰሩበት ናቸው። እነዚያ ትእዛዛቱን የሚፈፅሙ፣ ክልከከላውን የሚርቁ፣ ከወሰኑ የሚቆሙ እነሱ ናቸው የቁርኣን ሰዎች። እነዚህ የአላህ ሰዎች ናቸው፣ ከፍጡሩ ልዩዎቹ! ቁርኣንን አፍዞ፣ አሳምሮ የሚቀራና ሑሩፎቹን አስተካክሎ እያነበበ ነገርግን ድንጋጌዎችቹን የሚጥስ የሆነ ሰው ይሄ የቁርኣን ሰው አይደለም። ከአላህ ልዩ ሰዎች ውስጥም አይደለም። ይልቁንም ይሄ አላህና መልእክተኛውን የሚያምፅ ቁርኣንንም የሚፃረር ነው። አዎ።
የቁርኣን ሰዎች በተጨማሪ እነዚያ ማስረጃ የሚያደርጉት ናቸው። በማስረጃ አጠቃቀም ላይ በሱ ላይ ሌላን የማያስቀድሙ ናቸው። ፊቅሁንም አሕካሙንም በጥቅሉ ዲናቸውንም ከሱ ይወስዳሉ። እነዚህ ናቸው የቁርኣን ሰዎች።
【ሸርሑ ኪታቢ አልዑቡዲያህ】

ከ ወንድም Ibnu Munewor የተወሰደ።

Thursday, December 24, 2015

ያስፈልገዎታል!! ጀናባን የሚመለከቱ ህግና ደንቦች።

ከወንድም ኢብኑ ሙነወር የተወሰደ።

ያስፈልገዎታል!!
                         ጀናባን የሚመለከቱ ህግና ደንቦች

የቃላት መፍቻ፡-

1.   መኒይ (የዘር ፈሳሽ)፡-

- በስሜት ተስፈንጥሮ ከእርካታ ጋር የሚወጣ ፈሳሽ ነው፡፡
- ለወንድ ወፍራምና (ወደ ቢጫነት የሚያደላ) ነጭ ፈሳሽ ሲሆን ለሴት ደግሞ ቀጭንና ቢጫ ነው፡፡ [ሙስሊም፡ 311] ሽታው ወደሊጥ ሽታ የቀረበ ነው፡፡ በሆነ ምክንያት እነዚህ መታወቂያዎች ሊቀየሩ ይችላሉ፡፡
- ከወጣ በኋላ የሰውነት መቀዝቀዝ ዘና ማለት (ፉቱር) ይከተላል፡፡
- ፈሳሹ ሚዛን በሚደፋው የዑለማእ እይታ ጦሀራ እንጂ ነጃሳ አይደለም፡፡ ይህን የሚደግፉ ሶሒሕ ማስረጃዎች መጥተዋል፡፡ [ሙስሊም፡ 694] [አልኢርዋእ፡ 1/197]
- በውንም ይሁን በህልም ከወጣ ገላን መታጠብ ግዴታ ነው፡፡

2.   መዚይ፡-

- ግንኙነትን ሲታሰብ ወይም ሲፈለግ የሚወጣ ያዝ የሚያደርግ (የሚያጣብቅ)፣ ቀለም አልባ ቀጭን ፈሳሽ ነው፡፡
- አወጣጡ ከእርካታ ጋር አይደለም፡፡ ተስፈንጥሮ ስለማይወጣ መውጣቱ ላይስተዋል ይችላል፡፡
- ነጃሳ ስለሆነ የነካውን አካል ማጠብ ይገባል፡፡ ልብስን ግን የነካው ቦታ ላይ ውሃ በመርጨት ማፅዳት በቂ ነው፡፡
- የነካውን ቦታ እንጂ ገላን መታጠብ ግን ግዴታ አይደለም፡፡ ውዱእን ግን ያፈርሳል፡፡

3.   ወዲይ፡-

- ከሽንት በኋላ የሚወጣ ነጭ ሽታ አልባ ፈሳሽ ነው፡፡
- የሚያጣብቅ አይደለም፡፡
- ብይኑ ከሽንት ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡

4.   ከሴቶች ብልት የሚወጣ ፈሳሽ፡-

- ከማህፀን የሚወጣ ቀጭን ፈሳሽ ነው፡፡ መጠኑ ከሴት ሴት ይለያያል፡፡
- ሴቷ መውጣቱንም ላታስተውለው ትችላለች፡፡
- አካልንም ልብስንም ቢነካ አይነጅስም፣ ጦሃራ ነው፡፡
- ውዱእን ግን ያፈርሳል፡፡ ከሁለቱም መፀዳጃዎች በኩል የሚወጣ ነገር ውዱእ ያፈርሳልና፡፡ አወጣጡ ቋሚ ከሆነ ግን ለያንዳንዱ ሶላት ወቅቱ ከገባ በኋላ ውዱእ እያደረገች መስገድ ይገባል፡፡ ውዱእ ካደረገች በኋላ ቢወጣ ቦታም አይሰጠውም፡፡

                      ገላን መታጠብ ግዴታ የሚሆነው መቼ ነው?

1. በውኑ ግንኙነት ከተፈፀመ የዘር ፈሳሽ (መኒይ) #ቢፈስም_ባይፈስም ትጥበት ግዴታ ነው፡፡
2. ግንኙነት #ባይፈፀምም የዘር ፈሳሽ (መኒይ) #ከእርካታ ጋር ከወጣ ትጥበት ግዴታ ነው፡፡
3. በህልሙ ግንኙነት እንደፈፀመ አይቶ የዘር ፈሳሽ (መኒይ) ካገኘ በማያሻማ መልኩ መታጠብ ግዴታ ነው፡፡
4. በህልሙ ግንኙነት እንደፈፀመ አይቶ ነገር ግን ሲነቃ ምንም አይነት የዘር ፈሳሽ (መኒይ) ካላገኘ በማያሻማ መልኩ የመታጠብ ግዴታ የለበትም፡፡ ኡሙ ሱለይም የተባለችዋ ሶሐቢያህ ረዲየላሁ ዐንሃ “የአላህ መልእክተኛ ሆይ! አንዲት ሴት ኢሕቲላም ከሆነች (በህልሟ ግንኙነት ስትፈፅም ካየች) የመታጠብ ግዴታ አለባትን?” ብላ ስትጠይቅ “ፈሳሽ ካየች አዎ” ሲሉ መልሰውላታል፡፡ [ቡኻሪና ሙስሊም]
5. በህልሙ ግንኙነት ሲፈፅም አላየም ወይም አያስታውስም፡፡ ነገር ግን ሲነቃ የዘር ፈሳሽ (መኒይ) ካገኘ በማያሻማ መልኩ የመታጠብ ግዴታ አለበት፡፡
6. በህልሙ ግንኙነት ሲፈፅም አላየም ወይም አያስታውስም፡፡ ነገር ግን ሲነቃ ፈሳሽ አገኘ፡፡ የዘር ፈሳሽ (መኒይ) እንዳልሆነ እርግጠኛ ከሆነ የመታጠብ ግዴታ የለበትም፡፡ የነካውን ግን ሊያጥብ ይገባል፡፡ ብይኑ የሽንት ብይን ነውና፡፡
7. በህልሙ ግንኙነት ሲፈፅም አላየም ወይም አያስታውስም፡፡ ነገር ግን ሲነቃ የዘር ፈሳሽ (መኒይ) ይሁን አይሁን #መለየት_ያልቻለው ፈሳሽ ካገኘ በ ሽታ ወይም በቻለው መንገድ ለመለየት ይሞክርና ጥርጣሬው መኒይ ወደመሆኑ ካደላ ይታጠብ፡፡ ጥርጣሬው መዚይ ወደመሆኑ ካደላ ግን በተለይም ከመተኛቱ በፊት ስለ ግንኙነት አስቦ ከነበር እንደ መዚይ ይቁጠረውና የነካውን ቦታ ብቻ ይጠብ፡፡ ገላውን የመታጠብ ግዴታ የለበትም፡፡ ቢታጠብ ከጥንቃቄ አንፃር የተሻለ ነው፡፡
8. በህልሙ ግንኙነት ሲፈፅም አላየም ወይም አያስታውስም፡፡ ነገር ግን ሲነቃ የዘር ፈሳሽ (መኒይ) ይሁን አይሁን #መለየት_ያልቻለው ፈሳሽ ካገኘና ግምቱ ወደየትኛውም ካላደላ፣ ከመተኛቱ በፊት ስለ ግንኙነት #ያላሰበ ከሆነ ጉዳዩ አወዛጋቢ ቢሆንም ትክክለኛው ትጥበት የለበትም የሚል ነው፡፡ ቢታጠብ ከጥንቃቄ አንፃር የተሻለ ነው፡፡ [ፈታዋ ኢብኑልዑሠይሚን፡ 11/161]

የጀናባ አስተጣጠብ ሁለት አይነት ነው፡፡

1. የሚያብቃቃ ማለትም ግዴታውን ለማውረድ የሚጠበቅ ሲሆን እሱም ሙሉ አካልን በውሃ ማዳረስ ነው፡፡ ባይሆን መጉመጥመጥና በአፍንጫ ውሃ መሳብ (ኢስቲንሻቅ) እንዳይረስ፡፡ ለትጥበት ኒያ ሊዘነጋ አይገባም፡፡ አንድ ሰው ጀናባ ማውረድን ሳያስብ እንዲሁ ውሃ ውስጥ ዋኝቶ ቢወጣ መላ አካላቱ ውሃ መንካቱ ብቻ ጀናባው ለመውረዱ በቂ አይሆንም፡፡ ይስተዋል! ይህን ትጥበት ካደረጉ በኋላ ውዱእም ባያደርጉ መስገድ ይቻላል፡፡ ባይሆን ከትጥበቱ መሀል ውዱእ የሚያፈርስ ነገር መፈፀም የለበትም፡፡
2. ሌላኛውና በላጩ ግን በቅድሚያ ሁለት እጆችን መታጠብ፡፡ ከዚያም ኢስቲንጃእ ማድረግ፡፡ ከዚያም ውዱእ ማድረግ፡፡ ከዚያም ከእራስ ጀምሮ ቀሪ አካላትን ውሃ ማዳረስ፡፡ እግርን ከውዱእ ጋር ማጠብም ይቻላል፤ መጨረሻ ላይ ማጠብም ይቻላል፡፡ [ቡኻሪና ሙስሊም]

ማሳሰቢያ፡-

ሴቷ ለትጥበት ስትል የፀጉር ጉንጉኗን የመፍታት ግዴታ የለባትም፡፡ ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም: ኡሙ ሰለማህ ለጀናባህ ወይም ለሐይድ ትጥበት ፀጉሯን “ልፍታው ወይ?” ብላ ስትጠይቃቸው “አይ! የሚበቃሽ ከእራስሽ ላይ ሶስት ጊዜ ውሃ ማፍሰስ ብቻ ነው” ብለዋታል፡፡ [ሙስሊም] ስለዚህ ፀጉር ሳይፈታ ውሃ መድረስ ከቻለ መፍታት አይጠበቅም፡፡

ለማጣቀሻነት የተጠቀምኩት
1. ፈታዋ ኢብኑልዑሠይሚን
2. ፈትሑልዐላም ፊ ዲራሰቲ አሓዲሢ ቡሉጊልመራም እና ሌሎችም
ሼር ማድረግ እንዳይረሱ፡፡

(ኢብኑ ሙነወር፣ ህዳር 8/2008)

Friday, November 27, 2015

ኔትዎርክ ማርኬቲንግ በሸሪዓ እይታ



ኔትዎርክ ማርኬቲንግ በሸሪዓ እይታ 
Gold Quest,DXN, Tiens..etc in Sharia view
(አጭር መልእክት በኢልያስ አወል)

ይህ መልእክት ከአምስት አመታት በፊት የተቀረፀ አጭር መልእክት ሲሆን በተለየያዩ መድረኮች ይህ የግብይት ሲስተም ብዙ ጎጂ ጎኖች እንዳሉት በተደጋጋሚ ቢገለፅም በዚህ ስራ ላይ የሚገኙ ሰባኪዎች ሰዎችን ጠልፈው የነሱ ሰራተኛ ለማድረግ የሚያደርጉት እልህ አስጨራሽ ጥረት ብዙዎችን እየሸነገለ ነውና ይህንን ቪዲዮ ሼር በማድረግ ከወዲሁ ሰዎችን ከጥቃት እንታደግ።


በዚህ ዙሪያ ረዘም ያለ ትምህርት ለሚፈልጉ ከታች በሚገኘው ሊንክ በቅርቡ የተለቀቀውን ረጅም ማብራሪያ ዳውንሎድ ማድረግ ይችላሉ።

⇊ ⇊ ⇊ ⇊
ኔትዎርክ ማርኬቲንግ በሸሪዓ እይታ (New Audio) 
በኢኮኖሚክስ ምሁሩ ወንድማችን ኢልያስ አወል የተሰጠ ሞያዊና ሸሪዓዊ ትንተና

Download link 

ኔትዎርክ ማርኬቲንግ... 
ጎልድ ኩዌስት... ቲያንሽ እና ሌሎችም ፒራሚዳዊ ይዘት ያላቸው የግብይት ዘዴዎችነ የሚጠቀሙ ድርጅቶችን ትክክለኛ አሰራር እና ኢስላማዊ ብያኔያቸውን ያብራራል።

- ኢስላማዊ የግብይት ደንቦችና ስርዓቶች ባጭሩ 
- የፒራሚድዊ ኔትዎርክ አስራር ምን ይመስላል?
- የኢኮኖሚ ጠበብቶችና አለም አቀፍ ተቋማት እንዴት ያዩታል?
- የኢስላም ሊቃውንት አቋም ምን ይመስላል?

ሌላም ብዙ ይማሩበታል...

ላይክና ሼር በማድረግ ወገንን እናድን!

ከዚህ አይንቱ ኔትወርክ ሰለባዎች ተሞክሮዎችን በኮሜንቶችን እንጠብቃለን

Pyramid network marketing schemes like Gold Quest,DXN, Tiens..etc
in Sharia view

by Ilyas Awol


https://www.facebook.com/tenbihat/videos/845476205549924/?fallback=1

Saturday, October 24, 2015

8ኛ ሓዲስ : ወደ ተውሒድ ጥሪ ማድረግ፥ ሙስሊም ክብር እንዳለው።





الحديث الثامن
الدعوة للتوحيد وبيان حرمة المسلم
عَنْ ابْنِ عُمَرَ رَضِيَ اللَّهُ عَنْهُمَا، أَنَّ رَسُولَ اللَّهِ صلىاللهعليهوسلمقَالَ: "أُمِرْت أَنْ أُقَاتِلَ النَّاسَ حَتَّى يَشْهَدُوا أَنْ لَا إلَهَ إلَّا اللَّهُ وَأَنَّ مُحَمَّدًا رَسُولُ اللَّهِ، وَيُقِيمُوا الصَّلَاةَ، وَيُؤْتُوا الزَّكَاةَ؛ فَإِذَا فَعَلُوا ذَلِكَ عَصَمُوا مِنِّي دِمَاءَهُمْ وَأَمْوَالَهُمْ إلَّا بِحَقِّ الْإِسْلَامِ، وَحِسَابُهُمْ عَلَى اللَّهِ تَعَالَى" .
رَوَاهُ الْبُخَارِيُّ [رقم:25]، وَمُسْلِمٌ [رقم:22].


8ኛ ሓዲስ

የሓዲሱ ትርጉም

ወደ ተውሒድ ጥሪ ማድረግ፥ ሙስሊም ክብር እንዳለው።

ተሚም ኢብን አውስ አድ-ዳርይ በዘገበው ሓዲስ የአላህ መልእክተኛ صلى الله عليه وسلم እንዲህ አሉ። “ሰዎች በእውነት የሚመለክ ጌታ አንድ አላህ ብቻ ነው ሙሓመድን የአላህ መልእክተኛ ነው ብለው እስኪመሰክሩ፥ ሶላትን ቀጥ አርገው እስከሚሰግዱ እና ዘካን እስኪያወጡ ድረስ እንድጋደላቸው ታዝዣሎህ። እነዚህን ነገሮች ካደረጉ ግን ደሞቻቸውን እና ገንዘቦቻቸውን የእስልምና ሓቅ ሲቀር ከእኔ ይጠብቃሉ። ሒሳባቸውም አላህ ዘንድ ነው።”

ሓዲሱን ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል።



ከስምንተኛው ሓዲስ የምንወስዳቸው ትምህርቶች

1. ወደ ተውሒድ ጥሪ ማድረግ እንዳለብን።

2. ዘካን አልሰጥም ያለ ጦርነት እንደሚከፈትበት።

3. አንድ ሰው ከላይ እስልምናን ካሳየ ስለውስጡን አያገባንም። ሂሳቡ አላህ ዘንድ ነው።

4. ሰው እንደስራው ይመነዳል።መልካም ከሰራ በመልካም መጥፎ ከሰራ በመጥፎ።

5. ሙስሊም ክብር(ደሙ፣ ንብረቱ፣ ክብሩ) እንዳለው። 

Friday, October 2, 2015

የሶላታችንን ነገር አደራ! (ክፍል አንድ)



የሶላታችንን ነገር አደራ!

(ክፍል አንድ)

(ኢብኑ ሙነወር፣ መስከረም 19/2008) 
 
 ሶላት የዲን ምሰሶ የአማኞች ብርሃን ናት፡፡ ሶላት ከሁለቱ ሸሃዳዎች ቀጥሎ ቀዳሚዋ የኢስላም መሰረት ናት፡፡ በሶላት ጭንቆች ይወገዳሉ፡፡ ፈተናዎች ይታለፋሉ፡፡ ሶላት ለነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም የዐይን ማረፊያ፣ የእርካታቸው ቦታ ናት፡፡ ((ሶላት ከመጥፎና ከሚጠላ ነገር ሁሉ ትከለክላለች፡፡)) [አልዐንከቡት፡ 45] ሶላት ከላያችን ላይ ወንጀልን የምታረግፍ መጥረጊያ የሃጢኣት ቆሻሻን የምታፀዳ ወራጅ ውሃ ናት፡፡ [ሙስሊም]
ሶላት የማይሰግድ ሰው ምድቡ ከአማኞች ምድብ እንዳልሆነ የሚያመላክቱ እጅግ አስፈሪ የሆኑ ሐዲሦች ተላልፈዋል፡፡ እነዚህን ሐዲሦች መነሻ በማድረግም ሶላት የማይሰግድ ሰው “ሙስሊም ነው” “አይ አይደለም” በሚል በዑለማእ መካከል ጠንካራ የሀሳብ ልውውጥ አለ፡፡ አደጋ ላይ በመሆኑ ላይ ግን ቅንጣት ታክል ውዝግብ የለም፡፡ ኧረ እንዳውም “ሙስሊም ነው” ያሉት ሳይቀሩ “መገደል አለበት”፣ “መታሰር አለበት” … እያሉ ጥብቅ ሀሳብ የሰነዘሩት ቀላል አይደሉም፡፡ አንተ ከሶላት የተኳረፍከው ተላላ ሆይ! ይሄው የዲኑ ምሁራን “አንተ እጣ ፈንታህ ዘላለማዊ ቅጣት የሆነ ከሃዲ ነህ” በሚሉና “አይ ጥፋትህ ጫፍ የደረሰ፣ እጅግ አስፈሪ አደጋ የተደቀነብህ ጋጠ-ወጥ ሙስሊም ነህ” በሚል ጎራ ለይተው እየተወዛገቡብህ ነው!! ህሊና ካለህ ከዚህ በላይ ምን አስደንጋጭ ነገር አለ?!!
በርግጥ አሁን ርእሴ ከናካቴው ስለማይሰግድ ሰው አስፈሪ ሁኔታ መዘርዘር አይደለም፡፡ ይልቁንም የሶላት አሰጋገድ ህግና ደንቡን እንጠብቅ ዘንድ በስሱ ለማስታወስ ነው፡፡
አዎ መስገድ ብቻ ሳይሆን አሰጋገድን ማሳመርም ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ጌታችን አላህ ((ለሰጋጆች ወዮላቸው!)) ማለቱን አንዘንጋ፡፡ አዎ ((ለነዚያ ከሶላታቸው ተዘናጊዎች ለሆኑት!!)) [አልማዑን፡ 4-5] መልእክተኛው ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም የሶላት አሰጋገድን በቃልም አስተምረዋል፣ በተግባርም አሳይተዋል፡፡ ለዚህም ሲሉ ሚንበር ላይ ወጥተው እስከሚሰግዱ ደርሰዋል፡፡ ሚንበሩ ላይ ይቆማሉ፣ ሩኩዕ ያደርጋሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ ካጠናቀቁ በኋላ “ይህን የሰራሁት በኔ እንድትመሩ ነው፡፡ አሰጋገዴንም እንድትማሩ” ብለዋል፡፡ [ቡኻሪና ሙስሊም] እንዳውም ሶላትን በስርኣት ለሰገደ ከአላህ ብስራት ነግረውታል፣ እንዲህ ሲሉ፡- “አምስት ሶላቶችን በርግጥም አሸናፊውና የላቀው አላህ ደንግጓቸዋል፡፡ ውዱኣቸውን ያሳመረ፣ በወቅታቸው የሰገደ፣ ረኩዓቸውን፣ ሱጁዳቸው እና ኹሹዐቸውን ያሟላ ሰው በአላህ ላይ ሊምረው ቃል አለው፡፡ (እንዲህ) ያላደረገ ግን በአላህ ላይ ቃል የለውምና ከፈለገ ይምረዋል፣ ከፈለገም ይቀጣዋል፡፡” [ቡኻሪ]
አዎ የምናገኘው ያስገኘነውን ያክል ነው፡፡ “ሶላት መለኪያ ነች፡፡ መለኪያውን የሞላ ይሞላለታል፡፡ መለኪያውን ያጓደለ ግን ስለ ስፍር አጉዳዮች ምን እንደተባለ ታውቃላችሁ” ይላሉ ሰልማን አልፋሪሲ፡፡ ቀደምቶቻችን ከአንድ ሰው ዒልም ሊወስዱ ሲፈልጉ ቀድመው አሰጋገዱን ይመለከቱ ነበር፡፡ ሶላቱን በስርኣት ሲፈፅም ከተመለከቱት እሰየው! ካልሆነ ግን ለሶላቱ ታማኝ ያልሆነን ሰው እጃቸውን ከሱ ይሰበስቡ ነበር፡፡ በርግጥም ሶላት የአንድ ሙስሊም ስብእና ቀዳሚ መለኪያ ነች፡፡
እናም ለሶላታችን በምንሰጠው ዋጋና አፈፃፀም ልክ የምናገኘውም ደሞዝ ይለያያል፡፡ ይህን አስመልክተው ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እንዲህ ይላሉ፡- “በእርግጥም አንድ ባሪያ ሰላትን ይሰግድና ነገር ግን ከሷ አንድ አስረኛዋ (ወይም) አንድ ዘጠነኛዋ (ወይም) አንድ ስምንተኛዋ (ወይም) አንድ ሰባተኛዋ (ወይም) አንድ ስድስተኛዋ (ወይም) አንድ አምስተኛዋ (ወይም) አንድ አራተኛዋ (ወይም) ወይም አንድ ሶስተኛዋ (ወይም) ግማሹዋ እንጂ አይፃፍለትም” ይላሉ፡፡ [አልባኒ ሶሒሕ ብለውታል] ስለዚህ እንደ አሰጋገዳችን መለያየት የምናስመዘግበውም ምንዳ ይለያያል ማለት ነው፡፡ ስለሆነም ከሶላታችን በደንብ መጠቀም እንችል ዘንድ አሰጋገዳችንን ከነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም አሰጋገድ ጋር ለማመሳሰል መጣር ይጠበቅብናል፡፡ ለዚህም “ስሰግድ እንዳያችሁኝ ስገዱ” የሚለው የነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም መመሪያ ጥሩ ዋቢ ይሆነናል፡፡ [ቡኻሪ]
በአንድ በወቅት ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ከመስጂዱ አንድ ጥግ ላይ ሳሉ የሆነ ሰው መስጂድ ገባና መስገድ ያዘ፡፡ ሶላቱን ግን በጣም አሳጠራት፡፡ ሲጨርስም ከነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም ዘንድ መጣና ሰላምታን አቀረበ፡፡ እሳቸውም “ወዐለይከስሰላም፡፡ ተመለስና ስገድ፣ ምክንያቱም አንተ አልሰገድክምና” አሉት፡፡
ተመለሰና ሰገደ፡፡ ከዚያም ሰላምታ አቀረበ፡፡
አሁንም “ወዐለይከስሰላም፡፡ ተመለስና ስገድ፣ ምክንያቱም አንተ አልሰገድክምና” አሉት፡፡
በሶስተኛው ጊዜ ሰውየው እንዲህ አለ፡- “በሐቅ በላከህ ይሁንብኝ! ከዚህ ውጭ ማሳመር አልችልም፡፡ ስለሆነም አስተምረኝ” አላቸው፡፡
ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እንዲህ አሉት፡- “ለሶላት ስትዘጋጅ
ውዱእህን አሳምር፤
ከዚያም ወደ ቂብላ ተቅጣጭ፤
ከዚያም ‘አላሁ አክበር’ በል፤
ከዚያም ከቁርኣን የተገራልህን ቅራ፤
ከዚያም ሩኩዕ አድርግ፣ በሩኩዑህ ላይ እስከምትረጋጋ ድረስ፤
ከዚያም እራስህን (ከሩኩዕ) አቅና፣ ተስተካክለህ እስከምትቆም ድረስ፤
ከዚያም ሱጁድ ውረድ፣ በሱጁድህ ላይ እስከምትረጋጋ ድረስ፤
ከዚያም ከሱጁድ ተነስ፣ ቀጥ ብለህ እስከምትቀመጥ ድረስ፤
ከዚያም ሱጁድ ውረድ፣ በሱጁድህ ላይ እስከምትረጋጋ ድረስ፤
ከዚያም ተነስ፣ ተስተካክለህ እስከምትቆም ድረስ፤
ከዚያም ይህን (መረጋጋትህን) በሶላትህ በሙሉ ላይ ፈፅም፡፡
[ቡኻሪ፣ ሙስሊም፣ ኢብኑ ማጃህ፣ አልበይሀቂ፣…]
ከዚህ ክስተት እና የነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም እርማት ብዙ ቁም ነገሮችን መማር እንችላለን፡፡ ከምንም በላይ ግን “አልሰገድክም ተመለስ ስገድ” እያሉ ማመላለሳቸውን እናስምርበት፡፡ ከራሳችን ሶላትም ጋር እናነፃፅረው፡፡ በጥቅሉ ነብዩ ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም “ስሰግድ እንዳያችሁኝ ስገዱ” ያሉት፡፡ [ቡኻሪ] ሶላታችንን ከሳቸው ሶላት ጋር ለማመሳሰል አሰጋገዳቸውን ጠንቅቆ ማወቅ ይጠይቃል፡፡ አሰጋገዳቸው በተለያዩ የሱናህ ኪታቦች ላይ ሰፍሮ ይገኛል፡፡ በተለይም ደግሞ “ሲፈቱ ሶላቲንነቢይ” የሚለው የታላቁን ሙሐዲሥ የሸይኹልአልባኒይ ረሒመሁላህ ኪታብ በዚህ ረገድ እፁብ ድንቅ የሆነ ስራ ነው፡፡ እባኮትን በጥሞና አንብበው አሰጋገደዎን ይታዘቡ፡፡ በተግባርም ይጠቀሙት፡፡ ሌሎችንም ያስጠቅሙ፡፡ በአላህ ፈቃድ ከዚህ ኪታብ እና መሰል ስራዎች እየቀነጨብኩ እጅግ አንገብጋቢ ናቸው ብየ የማምንባቸውን በተከታታይ ለማቅረብ እሞክራለሁ፡፡

(ኢብኑ ሙነወር፣ መስከረም 19/2008)